Sunday, October 26, 2014

በአገር ላይ የሚመጣ አደጋን አቅልሎ የማየት ያልሰለጠነ አስተሳሰብ




(ኤፍሬም እሸቴ) 
ታዳጊ አገሮችን በሙሉ የሚያመሳስላቸው አንድ ግርም የሚለኝ ነገር ከገደል አፋፍ ቆሞ ገደሉን መናቅ፣ ከአደጋ ጫፍ ቆሞ አደጋን ማቃለል፤ ከዚያም ከገደሉ ወድቆ መሰበር፣ በአደጋው ተጠራርጎ መወሰድ። ይህ ሐሳብ በርግጥ ፍንትው ብሎ የታየኝ የማሌዢያ አውሮፕላን በዩክሬይን ሰማይ ላይ በሚሳኤል በጋየበት ጊዜ ነበር። ሁላችሁም እንደምታስታውሱት የሰው አካል ቁርጥራጭ ከሰማይ ይዘንብ እንደነበር እማኞች ሲናገሩ መልክተናል። ታላላቆቹ የዜና አውታሮች ራሺያ ላይ አተኩረው ነገሩን በዚያ ፈፀሙት አንጂ “አውሮፕላኑ በጦርነት ሰማይ ላይ ለምን ሄደ?” የሚለውን የሚያነሱ ሰዎችም ተደምጠዋል። ብዙ አየር መንገዶች አቅጣጫቸውን ቀይረው በሌላ መስመር መሔድ ከጀመሩ ቆይተው ነበር። የሳንቲም ስባሪ ለማትረፍ አንድም በማሌዢያኛ “አቦ አታካብዱ” ብለው ሳይሆን አይቀርም በዚያ በታዳጊ አገር አስተሳሰብ መንገዳቸው ሳይቀይሩ ቀሩ። “የእባብ ጉድጓድ በጅል ክንድ ይለካል” እንደሚባለው የዩክሬይን አየር በማሌዢያ አውሮፕላን ክንድ ሲለካ ጅልም እጁ አይተርፍ፣ አውሮፕላኑም አልተረፈ። ተመሳሳይ ነገር እነሆ ሊከሰት ነው። ኢትዮጵያ በበኩሏ 200 ነርሶች ወደ ኢቦላ ዞን (Ebola ZOne) ልትልክ ጀብደኛ ውሳኔ ወስናለች። የማሌዢያ ውሳኔ። ኢቦላ ምዕራብ አፍሪካን ምን እያደረገ ነው? ከበሽተኛው በሚወጣ ፈሳሽ በሚተላለፈው በዚህ በሽታ የአገራች ኢኮኖሚ እንዴት እንዴት እየሆነ ነው? የዚያ አገር ዜጋ የሆኑ በማለው ዓለም የሚኖሩ ሰዎች እንዴት እየታዩ ነው? ምን ዓይነት ችግር እየገጠማቸው ነው? አይበለውና በሽታው አገራችን ቢገባ ዘመዶቹን በማስታመም የሚታወቅ የአገራችን ሰው እንዴት ባለ አደጋ ላይ ይወድቃል? የትኛው ሆስፒታል በርግጥ ብቁ ነው? መቸም በፌዴራል ፖሊስ ዱላ አታስቆሙት ነገር።“የሕዳር በሽታን” በአገራችን በ21ኛው ክ/ዘመን ልታመጡብን ካልሆነ በእውነቱ ምን ሌላ ምክንያት ይኖራችኋል? በዓለም ላይ በሕክምና አያያዛቸው ጥራት የተመሰገነላቸው ብዙ አገሮች አሉ። ኢቦላን በረዓድ እያዩት ነው። ሕዝቡ ገና ስሙን ሲሰማ ሽብር ይይዘዋል። አንድ ሰው ቴክሳስ ግዛት በበሽታው በመሞቱ መላው አሜሪካ ከሥሩ ነው የተነቃነቀው። በርግጥ እነርሱ ፈሪዎች ስለሆኑ እኛ ጀግንነት ይዞን ይሆን? የሚመጣውን ጉድ ስለሚረዱት ነው። ይህንን ያልሰለጠነ አስተሳብ እንዴት ማስለቀቅ ይቻል ይሆን? አለመሰልጠን ወንጀል አይደለም ነገር ግን አገር ላይ ሊያመጣ የሚችለውን አደጋ እያወቁ ለጋ ወጣቶችን ወደ እሳት መላክ ግን ሌላ ዓላማ እንዳለው ነው የሚረዳኝ። ምናልባት በበሽታው የሚገኝ ትርፍ እንዳለ እንጃ። ፈጣሪ ሕዝቡን ይታደገዋል። ለእናንተ ግን እንጃ!!! - 


Link:-http://www.zehabesha.com/amharic/archives/35726

No comments:

Post a Comment

Note: Only a member of this blog may post a comment.